ክፍለ ጊዜ 7/21

ገጽ 2/5 የርዕስ መግቢያ፡- ህጻናት ሰውን በማጣታቸው ምላሽ የሚሰጡበት መንገድ

የርዕስ መግቢያ፡- ህጻናት ሰውን በማጣታቸው ምላሽ የሚሰጡበት መንገ

ህጻኑ ከወላጆቹ ተነጥሎ የአደራ ቤተሰብ እንክብካቤ እንዲያገኝ የተመደበበትን ዕድሜ መሠረት በማድረግ ህጻናት ሰውን ሲያጡ ምላሽ የሚሰጡበት እና የሚሰማቸውን ከባድ ሀዘን የሚገልጹበት መንገድ የተለያየ ነው። በተጨማሪም የሚሰማቸውን ከባድ ሀዘን ለመቋቋም ጥረት የሚያደርጉባቸው የተለያዩ መንገዶች አሏቸው። ሰዎች አብዛኛውን ጊዜ ወላጅን ስለማጣት ሲያወሩ “ችግሩን ጊዜ ይፈታዋል” ይላሉ፤ ነገር ግን ይህ የሚሰራው ከወላጃቸው ወይም ትልቅ ቦታ ከሚሰጡት እና በጣም ከሚቀርቡት ሌላ ሰው ጋር በተለያዩበት ጊዜ በጣም ትንሽ ዕድሜ ላይ ለነበሩ ህጻናት ብቻ ነው። አንድን ሰው ማጣት ሲባል የግድ የወላጅ ሞት መሆን አለበት ማለት ሳይሆን በአካል መለያየት ራሱ ሊሆን ይችላል። በተጨማሪም አንድ ወላጅ ከህጻኑ አጠገብ ቢሆንም ለምሳሌ በእናቶች ላይ በሚከሰት ድባቴ፣ በአእምሮ በሽታዎች ወይም እንክብካቤ ሰጪው ራሱ ልጅ እያለ በቂ እንክብካቤ ያላገኘ በመሆኑ የተነሳ ምላሽ ለመስጠት ላይችል ይችላል።በተጨማሪም ህጻኑ የሚኖረው የስሜት ለውጥ ርዝመት እና ክብደት አዲሶቹ እንክብካቤ ሰጪዎች እንደሚሰጡት ቅርበት ይወሰናል።

የተፈጥሮአዊ መቃወም ምዕራፍ – ስሜት የማይነበብበት ፊት ሙከራ

አብዛኛውን ጊዜ ህጻናት ከሰው ጋር በሚለያዩበት ወይም ምላሽ በማያገኙበት ወቅት የመቃወም ምዕራፍ ውስጥ ያልፋሉ፡- ያለቅሳሉ፣ ምቾት አይሰማቸውም እንዲሁም ለማባበል ያስቸግራሉ፣ አዲሶቹ የአደራ ቤተሰብ ወላጆቻቸው ሊያቀርቧቸው የሚያደርጓቸውን ጥረቶች አንቀበልም ሊሉ ይችላሉ። በእርግጥ ይህ መደበኛ እና ጤናማ ምላሽ ነው፡- ተጨማሪ መለያየት እንዳይከሰት ለመከላከል የህጻኑ ሰውን በጣም የመቅረብ ሥርዓት መሥራት ባለበት መልኩ እየሰራ መሆኑን የሚያሳይ ነው።ይህ ምላሽ በተግባር ምን እንደሚመስል በዶ/ር ኤድ ትሮኒክ የተከናወነው “ስሜት ማይነበብበት ፊት ሙከራ” ላይ ማየት ትችላላችሁ። መጀመሪያ ላይ እናትየው ምላሽ ትሰጣለች እንዲሁም ትብብር ታሳያለች፤ ከዚያ ፊቷን ስሜት የማይነበብበት እንድታደርገው ትጠየቃለች። ህጻኑ ወዲያውኑ ትኩረቷን ለማግኘት መሞከር ይጀምራል፣ ተስፋ የመቁረጥ ስሜት ይሰማዋል እንዲሁም መጨረሻ ላይ ያለቅሳል።ምላሽ መስጠት የማትችል እናት ያለችው ህጻን እንዴት ከመጠን በላይ የሆነ ጭንቀት እንደሚሰማው መገመት ትችላላችሁ፡-
ከ0-24 ወራት ዕድሜ ላይ ያሉ ህጻናት ለመለያየት የሚሰጡአቸው ከባድ ምላሾች፡- መደንዘዝ (WTHDRAWAL) ወይም ከመለያየት ጋር የተያያዘ ጠቅላላ ጭንቀት (GENERALIZED SEPARATION ANXIETY)

ሰውን በጣም የመቅረብ ባህሪ ያለመኖር፡-  መለያየት ከተከሰተ በኋላ ሌላ በጣም የሚቀርቡት ሰው ካልቀረበ ወይም እንክብካቤ ሰጪዎች ለህጻኑ ለቅሶ ምላሽ ካልሰጡ ህጻኑ ማልቀስ ሊያቆም እና ሲታይ የተረጋጋ፣ ግድ የማይሰጠው እና የደነዘዘ ሊመስል ይችላል። ይህ ግን እንዲያውም የአደጋ ምልክት ነው፡- ሰውን የመቅረብ ሥርዓቱ ሥራውን አቁሞ ሊሆን ይችላል ነገር ግን ህጻኑ ቋሚ የሆነ የሀዘን ስሜት ውስጥ ሊሆን ይችላል። ለማቅረብ እና ለማጽናናት ለሚደረጉ ጥረቶች የሚሰጠው ምላሽ ሊቀንስ ወይም ከነጭራሹ ምላሽ ላይሰጥ ይችላል። ይህ ወደ ድባቴ እና መደንዘዝ ሊቀየር እና በዚያ የተነሳ ህጻኑ ላይጎለብት ወይም በበቂ ሁኔታ ላያድግ ይችላል። ይህ ባህሪ ትንሽ ዕድሜ ላይ እያሉ እንክብካቤ ሰጪዎቻቸው ወይም በጣም የሚቀርቧቸው ሰዎች በተደጋጋሚ ሲቀያየሩ ባዩ ህጻናት እና ለምሳሌ በህጻናት ማሳደጊያዎች ወይም በሆስፒታሎች ውስጥ በጣም ትንሽ መስተጋብር ያገኙ ህጻናት ላይ የተለመደ ነው። 

ለመለያየት የተጋነነ ምላሽ መስጠት፡–  ወይም መለያየቱ የተከሰተው በድንገት ከሆነ እና አስደንጋጭ ከሆነ (ምን አልባት ህጻኑ ወላጆቹ እያለቀሱ እና እየተጣሉ በባለሥልጣን አካላት እና በፖሊስ ተወስዶ ሊሆን ይችላል) ህጻኑ በአጠቃላይ ጭንቀት እና ከመለያየት ጋር የተያያዘ የመረበሽ ስሜት ሊፈጠርበት ይችላል። ምን አልባትም የህጻኑ ሰውን በጣም የመቅረብ ሥርዓት ትንሽ ዕድሜ ላይ እያለ ባጋጠመው አንድ ወይም ከዚያ በላይ አስደንጋጭ ክስተቶች የተነሳ ከመጠን በላይ ስሜቱ ቅርብ እና “ከመጠን በላይ ንቁ” ሊሆን ይችላል። ስለዚህ ከክፍሉ በወጣችሁ ወይም ዞር ባላችሁ ቁጥር ህጻኑ እጅግ በጣም ሊፈራ እና ሊረበሽ እንዲሁም ባላችሁበት ቦታ እንደምትቆዩ በተደጋጋሚ እንድታረጋገጡለት ሊፈልግ ይችላል። መለያየት በጣም በቀላሉ ስሜታቸውን እንዲጎዳው የሆኑ ህጻናት ሁል ጊዜ ይዘዋችሁ አልለቅ ሊሉ፣ ከመተኛት ጋር በተያያዘ ከፍተኛ ችግር ሊኖርባቸው እንዲሁም ለአጭር ጊዜ መደበኛ በሆነ መልኩ በሚለያዩበት ጊዜም እንኳን ማስተማመን እና ማጽናናት ሊያስፈልጋቸው ይችላል። ይህ የአደራ ቤተሰብ እንክብካቤ እንዲያገኙ የተመደቡ ህጻናት በመጀመሪያው ምዕራፍ ወቅት በተደጋጋሚ የሚያጋጥማቸው ችግር ነው። 

የማሰላሰያ እና የመወያያ ጥያቄዎች

  • እናንተ ጋር ከተመደበ በኋላ የአደራ ልጃችሁ ላይ የመደንዘዝ ወይም መለያየትን ከመጠን በላይ የመፍራት ሁኔታ አይታችሁበታል?
  • ምን ያህል ጊዜ ቆየ (አሁን አቁሟል ወይም ቀለል ብሏል)?
  • ለልጁ ባላችሁ ስሜት ላይ ምን ዓይነት ተጽዕኖ አሳድሯል?
  • እንክብካቤ ሰጪ እንደመሆናችሁ መጠን ድባቴ ውስጥ ገብታችኋል ወይም የማትፈለጉ የመሆን ስሜት ተሰምቷችኋል?
  • ህጻኑ መለያየትን ከመጠን በላይ መፍራቱ ህጻኑን ለደቂቃ ያህል ለብቻው እንደመተው ባሉ ሁኔታዎች መደበኛ በሆነ መልኩ ለአጭር ጊዜ እንዳትለዩት ፍርሀትን ፈጥሮባችኋል?
  • ህጻኑ ለእናንተ ምላሽ ያልሰጣችሁ ከሆነ ወይም ካለማቋረጥ ይዟችሁ አልለቅም እያለ እና ከክፍሉ ስትወጡ እየፈራ ከነበረ ምላሻችሁ ምን ዓይነት ነበር?