ክፍለ ጊዜ 18/21

ገጽ 2/4 ርዕስ ሀ፡- በልጆቻቸው ዕድገት ውስጥ እንዲሳተፉ አባቶችን የግድ ማገዝ ያለብን ለምንድን ነው?

ርዕስ ሀ፡- በልጆቻቸው ዕድገት ውስጥ እንዲሳተፉ አባቶችን የግድ ማገዝ ያለብን ለምንድን ነው?

በምስራቅ አፍሪካ ሰዎች መንደሮችን ለቀው እየሄዱ በከተሞች እና ድህነት ባለባቸው ሰፈሮች በመኖር ላይ ያሉ ሲሆን እነዚህ ስፍራዎች በሥራ አጥነት የተነሳ ድህነት እና ተስፋ መቁረጥ ያለባቸው ናቸው። በተጨማሪም ኮቪድ-19 የፈጠረው ቀውስ የቤተሰብ ግንኙነቶች ላይ ባሳደረው ጫና የተነሳ ከአባታቸው ጋር ግንኙነት ያቋረጡ ህጻናት ቁጥር ጨምሯል።

ከመንደሮች ወደ ከተሞች የሚደረገው ፍልሰት በባህሉ መሠረት ከአባት በሚጠበቁ ነገሮች እና በተጨባጭ ባለው አዲስ ሁኔታ መካከል ግጭት እንዲፈጠር ምክንያት ሆኗል። አብዛኛዎቹ ወንዶች እና ሴቶች አሁንም ያላቸው አስተሳሰብ ባህላዊ ነው፡- ዋነኛው የአባት የሥራ ድርሻ ለቤተሰቡ የሚያስፈልጉትን ነገሮች የሚያሟላ የቤተሰቡ የገቢ ምንጭ መሆን ነው የሚል ማለት ነው። ስለዚህ በሥራ አጥነት የተነሳ ይህን ማድረግ በሚያቅተው ጊዜ በሴቶች ላይ ጥላቻን እና መከፋትን እንዲሁም በወንዶች ላይ ለራስ ዝቅተኛ ግምት መስጠትን ይፈጥራል። በርካታ አባቶች ተስፋ እንደሚቆርጡ፣ ቤተሰቡን ትተው እንደሚሄዱ ወይም ዕፅ ወደመጠቀም እንደሚገቡ በምስራቅ አፍሪካ የተከናወኑ ጥናቶች ያሳያሉ። አንዳንዶቹ ሚስት ያገቡ እና ልጆቻቸው የሚያስፈልጓቸውን ነገሮች ማሟላት ባለመቻላቸው ሀፍረት ስለሚሰማቸው ልጅ ከወለዱ በኋላ ብዙም ሳይቆዩ ፍቺ ይፈጽማሉ። ይህም በርካታ ህጻናት እና ወጣቶች ያለአባት እንክብካቤ እና ጥበቃ እንዲያድጉ ምክንያት ሆኗል። በታንዛኒያ እና ኬንያ ካሉ ህጻናት ውስጥ አንድ ሦስተኛው የሚያድጉት ያለአባት ሲሆን ይህም ለዕድገታቸው ከፍተኛ አደጋን የሚፈጥር ነው። በሩዋንዳ ካሉ ቤተሰቦች ውስጥ አንድ ሦስተኛው ያለአባት ልጃቸውን በሚያሳድጉ እናቶች የሚተዳደሩ ሲሆኑ ከአምስት ቤተሰቦች ውስጥ አንዱ በአያት ወይም ዕድሜው ገፋ ባለ ዘመድ የሚተዳደር ነው።

የድሮው ደንብ (አባቶች ስኬታማ የሚባሉት ከፍተኛ ገቢ ካላቸው ብቻ ነው የሚለው) ለአብዛኛዎቹ ወንዶች የማይቻል በመሆኑ በርካታ አባቶች ተስፋ እንዲቆርጡ እና ቤተሰባቸውን ጥለው እንዲሄዱ ምክንያት ሆኗል። ነገር ግን ጥናቶች እንደሚያሳዩት ከሆነ የአንድ አባት ገቢ የማህበራዊ እና ስነ-ልቦናዊ ተሳትፎውን ያህል አስፈላጊ አይደለም። አባቶች ከህጻናት እና በአሥራዎቹ ዕድሜ ውስጥ ካሉ ልጆቻቸው ጋር ባሏቸው ግንኙነቶች ውስጥ ሲሳተፉ ልጆች በትምህርት ላይ የሚያሳዩት ብቃት እና የዕድሜ ልክ ዕድገታቸው በጣም የተሻለ ይሆናል። ይህ ወሳኝ መልዕክት ሊዳረስ እና አባቶችን እንዲያበረታታ እና እንዲደግፍ የአካባቢውን ማህበረሰብ ሊያነሳሳ የሚችለው እንዴት ነው? አባቶች ለልጆቻቸው ምን ያህል አስተዋጽዖ ማድረግ እንደሚችሉ እንዲገነዘቡ በማድረግ ተስፋቸውን እና ኩራታቸውን መልሰን መገንባት የምንችለው እንዴት ነው?

ምሳሌ፡- ሚሂጎ በማህበረሰቡ ውስጥ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ሥራ ያለው የተካነ የመኪና መካኒክ ነበር። ለሚስቱ እና ለሦስት ልጆቹ የሚያስፈልጓቸውን ነገሮች ያሟላላቸው ነበር። አንድ ቀን ከመኪና ስር ተኝቶ እየሰራ እያለ የመኪናው ድጋፍ በመሸሹ ክንዱ ላይ ጉዳት ደረሰበት። ከዚያም የሚሰራው አንድ እጁ ብቻ የነበረ በመሆኑ ገቢውን አጣ፤ ተስፋ በመቁረጡም ቤተሰቡን ጥሎ በመሄድ መጠጣት ጀመረ። በኤስ ኦ ኤስ ሰራተኞች አነሳሽነት ጓደኞቹ እና ጎረቤቶቹ ባለቤቱን ረዷት እና እሱንም ፈልገው አገኙት። መጀመሪያ ላይ በማፈሩ የተነሳ የእነሱን እርዳታ አልቀበልም ብሎ ነበር፤ ነገር ግን አይሆንም ብለው ምን ያህል ቦታ እንደሚሰጡት ማሳየታቸውን ቀጠሉ። ባለቤቱ እና ልጆቹም የእሱ ፍቅር እና እንክብካቤ ለእነሱ ምን ያህል ትልቅ ቦታ እንዳለው ነገሩት። እነሱ ባደረጉለት እንክብካቤ በመታገዝ ከባለቤቱ እና ከልጆቹ ጋር መልሶ ሊገናኝ ችሏል። ምን ያህል እንደሚፈለግ በማወቁም ከቤተሰቡ ጋር በመሆን ተንቀሳቃሽ ጋሪ በመግዛት የመንገድ ላይ ንግድ ለመጀመር መሥራት ችለዋል።

አባቶች ለህጻናት ዕድገት አስፈላጊ ናቸው የሚለውን ዕውቀት ማስፋፋት የምትችሉት እንዴት ነው?

በማህበረሰቡ ውስጥ የእናንተ የሥራ ድርሻ፡- ስለ አባቶች ተሳትፎ አዎንታዊ ግንዛቤን ማስፋፋት

የእናንተ የሥራ ድርሻ የማህበረሰብ ስብሰባዎችን መጋበዝ እና መምራት እና አባቶች በቤተሰባቸው ውስጥ መሳተፋቸው የሚያስገኛቸውን ከፍተኛ አዎንታዊ ውጤቶች ማሳወቅ ነው። የማህበረሰብ የቡድን ውይይቶችን እና ሀሳቦችን በማነሳሳት እንዲሁም ተስፋን እና የማህበረሰብ አገልግሎቶችን በመፍጠር አባቶችን ለማጠናከር ክህሎቶቻችሁን እና ልምዳችሁን ተጠቀሙ።

ሠራተኞች እንደመሆናችሁ መጠን ከሥራ አንጻር አባቶች የሚገኙበትን ጠቅላላ ሁኔታ መለወጥ አትችሉም። ነገር ግን አባቶች በቤተሰብ ህይወት ውስጥ መሳተፋቸው ገንዘብ ያላቸው ከመሆን እጅግ የበለጠ ቦታ ያለው ስለመሆኑ ግንዛቤ ልትፈጥሩ ትችላላችሁ። አንድ አባት ድሀ ቢሆንም እንኳን የሚያደርገው ማህበራዊ እና ስነ-ልቦናዊ ተሳትፎ በአዋቂነት ህይወት ውስጥ የስኬት መሰረት የሆኑትን የህጻናትን መሰረታዊ ዕሴቶች በመገንባት ረገድ እጅግ በጣም አስፈላጊ ነው። ለምሳሌ ኔልሰን ማንዴላ አባታቸው የሞቱት ዕድሜአቸው 12 ዓመት እያለ ነበር፤ ነገር ግን “የሚኮሩበትን አመጸኝነታቸውን እና ፍትህ ማወቅን” የተማሩት ከአባታቸው እንደሆነ በኋላ ላይ ማንዴላ ጽፈዋል። ለዚህ ክፍለ ጊዜ ባደረግናቸው ቃለ መጠይቆች ምንም እንኳን ብዙ ተግዳሮቶች ቢያጋጥሟቸውም በየቀኑ ቤተሰባቸውን የሚንከባከቡ በርካታ አባቶችን ያገኘነውን ያህል ተስፋቸውን እና ኩራታቸውን ያጡ በርካታ አባቶችንም እንዲሁ አግኝተናል። ከማህበረሰባቸው የሚያገኙትን ድጋፍ ለመገንባት ዕውቀት እና መነሳሳት ያስፈልጋቸዋል። በሀፍረት ከመደበቅ ይልቅ ኃላፊነት የሚወስዱ አባቶች መሆንን በመምረጣቸው ሊበረታቱ ይገባል።

“አባት” ማለት ማን ነው?

በዚህ ፕሮግራም ውስጥ አባት ማለት ለቤተሰቡ ኃላፊነት ለመውሰድ የሚሰራ ወይም እንደዚያ እንዲያደርግ ሊበረታታ የሚችል ማንኛውም ወንድ ነው። የአባት የሥራ ድርሻ በተፈጥሮ አባቶች ሊከናወን ይችላል፤ ነገር ግን በሌሎች ወንዶችም ሊከናወን ይችላል። በአፍሪካ ባህል መሠረት አባት ወይም “አባባ” የሚለው እንደ ወንድ አያቶች፣ ታላቅ ወንድሞች ወይም የአጎት/የአክስት ልጆች ያሉ በማህበራዊ ትስስሩ ውስጥ ያሉ ወንዶችን በአጠቃላይ የሚገልጽ ነው። ይህ ልዩ ማህበራዊ ትስስር ለህጻናት ጥበቃ የሚያደርግላቸው እንደሆነ ጥናቶች የሚያሳዩ በመሆኑ ይበልጥ እንዲያጠናክሩት ማህበረሰቦችን ልታነሳሱ ትችላላችሁ። የአባቶች ተሳትፎ ለህጻናት ያለውን ትልቅ ዋጋ ከመመልከታችን በፊት እባካችሁ የሚከተሉትን ጥያቄዎች ለራሳችሁ አሰላስሏቸው፡-

 

  • በማህበረሰባችሁ ውስጥ ስላሉ አባቶችች ያሏችሁ የራሳችሁ እይታዎች ምንድን ናቸው?
  • ለአባቶች በቤተሰባቸው ውስጥ መሳተፍን እና ከባለቤታቸው እና ከልጆቻቸው ጋር መግባባትን ከባድ የሚያደርግባቸው ነገር ምንድን ነው?
  • አባቶች ቤተሰባቸውን ስለመንከባከብ ችሎታቸው ምን ይላሉ?
  • በሥራችሁ የምትደግፏቸው ህጻናት እና ወጣቶች፡- ከአባታቸው ጋር ስላላቸው ግንኙነት ምን ይላሉ?
አባቶች ለአዎንታዊ የህጻናት ዕድገት በጣም አሰፈላጊ የሆኑት ለምንድን ነው?
የአባት ተሳትፎ ሊያስገኛቸው ስለሚችላቸው አዎንታዊ ውጤቶች ከምስራቅ አፍሪካ ጥናቶች የተገኙ ውጤቶችን በምታነቡበት ወቅት ንቁ ተሳትፎ ስለሚያደርግ አባት ሰዎች ያላቸውን ግንዛቤ ለማዳበር እና እምነታቸውን መልሶ ለመገንባት ይረዳሉ ብላችሁ ስለምታስቧቸው ክርክሮች አስቡ። እነዚህ አዎንታዊ ውጤቶች አብረው መኖር ያቆሙ ቢሆንም እንኳን ለልጃቸው ሲሉ መስማማት እና ተጋግዘው መስራት ላይ ጎበዝ የሆኑ ወላጆችንም እንዲሁ ይመለከታሉ። በተጨማሪም የእንጀራ አባቶችን እና እንደ የአባት ምትክ የሚያገለግሉ ዘመዶችን ይመለከታሉ። አንድ አባት ሀብታም ወይም ድሀ መሆኑ ለውጥ ያመጣል፤ ነገር ግን ከዚያ በላይ በጣም ዋናው ነገር ማህበራዊ እና ስነ-ልቦናዊ እንክብካቤ ለማድረግ ያለው ፈቃደኝነት እንደሆነ ጥናቶች ያሳያሉ።

አባቶች ልጆቻቸውን በመንከባከብ ውስጥ ሲሳተፉ የልጆቹ ህይወት በከፍተኛ ሁኔታ የተሻለ ይሆናል፡-

  • አነስተኛ ዕድሜ ላይ ባሉ ህጻናት ጤና፣ ደህንነት እና እንክብካቤ ላይ ተጽዕኖ የሚያሳድሩ በርካታ ውሳኔዎችን የሚወስኑት አባቶች ናቸው
  • አባት እና እናት ያሉባቸው ቤተሰቦች ከገንዘብ አንጻር አንድ ወላጅ ካለባቸው ቤተሰቦች የተሻሉ ናቸው
  • ከባላቸው ጋር የሚኖሩ እናቶች አብዛኛውን ጊዜ ያለባቸው ጭንቀት አነስተኛ ነው
  • ከአባት ጋር ያላቸው ግንኙነት ህጻናትን ከጉዳት እና ከጥቃት ይጠብቃቸዋል
  • ከአባት ጋር የቅርብ ግንኙነት ያላቸው ልጆች ትምህርታቸው ላይ ይበልጥ ጎበዝ ናቸው
  • በተጨማሪም ያሉባቸው የስነ-ልቦና እና የባህሪ ችግሮች በአንጻሩ ያነሱ ናቸው
  • ተሳትፎ የሚያደርግ አባት ያለባቸው ቤተሰቦች ውስጥ ያሉ ሴት ልጆች ለራሳቸው ያላቸው ግምት እና በራስ የመተማመን ስሜታቸው ከፍተኛ ነው

በተጨማሪም በተለይ ወንድ ልጆች የአባታቸውን አመራር፣ ምክር እና ቅርበት እንደሚናፍቁ ጥናቶች ያሳያሉ። በአሥራዎቹ ዕድሜ ውስጥ ያሉ ወንድ ልጆችን እና የወጣት ወንዶችን የወደፊት ዕጣ ፈንታ በአብዛኛው የሚወስነው እንደ አርአያ ከሚያዩት ወንድ ጋር የሚኖራቸው የቅርብ ግንኙነት እና የሚያደርጓቸው ውይይቶች ናቸው። በተጨማሪም ህጻን እና ወጣት ልጆቻቸውን በመንከባከብ ውስጥ መልሰው መሳተፍ ወይም መሳተፍ ለአባቶች ከፍተኛ የኩራት እና የኃላፊነት ስሜት ይሰጣቸዋል እንዲሁም በማህበረሰቡ ውስጥ ዕውቅና ያስገኝላቸዋል።

ስለዚህ የሚከተለውን እንመልከት፡- የአባት ተሳትፎ ማለት ምንድን ነው?

አባት በልጅ ህይወት ውስጥ የሚያደርገው አዎንታዊ ተሳትፎ የሚያካትታቸው አራት ነገሮች

ምንም አንኳን አንድ አባት ድሀ ወይም ሥራ አጥ ቢሆንም ተሳትፎ የሚያደርግ ከሆነ በቤተሰቡ እና በልጆቹ ደህንነት ላይ ከፍተኛ ለውጥ ማምጣት ይችላል። “ተሳትፎ” ማለት ምንድን ነው?

የአባት ተሳትፎ የሚከተሉትን አራት ነገሮች ያካትታል፡-

  • ቶሎ ቶሎ መስተጋብሮችን ማድረግ። አባትየው አብዛኛውን ጊዜ በጨዋታ፣ በዕለት ተዕለት ንግግሮች፣ ውይይቶች እና ግጭቶችን በመፍታት ውስጥ ይሳተፋል እንዲሁም ለህጻናት እና በአሥራዎቹ ዕድሜ ውስጥ ላሉ ልጆቹ የመሪነት ሚናን ይጫወታል።

  • መገኘት። ህጻናትና እና በአሥራዎቹ ዕድሜ ውስጥ ያሉ ልጆቹ ድጋፍ እና ምክር ሲፈልጉ አባትየው ለማዳመጥ፣ ለመወያየት እና ምላሽ ለመስጠት ዝግጁ መሆኑን ያሳያል። አብዛኛውን ጊዜ ሌሎች ነገሮችን በመተው ጊዜ ይሰጣል እንዲሁም አብዛኛውን ጊዜ ህጻን እና በአሥራዎቹ ዕድሜ ውስጥ ያለ ልጁ ችግር ካጋጠመው ያልተከፋፈለ ትኩረት ይሰጣል  ፍላጎትም ያሳያል።

  • ኃላፊነት። አባትየው የህጻኑን ዕድገት በሚመለከቱ የቤተሰብ ክርክሮች እና ውሳኔዎች ውስጥ ይሳተፋል። ለምሳሌ፡- ትምህርትን በማቀድ ሂደት ውስጥ በአሥራዎቹ ዕድሜ ውስጥ ያሉ ልጆችን ከአደጋ ወይም መጥፎ አርአያ ከሚሆኑ ሰዎች መጠበቅ፣ ከጤና እና ከክትባት ጋር በተያያዙ ቀጠሮዎች ውስጥ በመሳተፍ፣ ወዘተ። አርአያ እንደመሆኑ መጠን የሞራል እሴቶቹን ለልጆቹ ያስተላልፋል እንዲሁም የህይወትን ተግዳሮቶች እንዴት መወጣት እና ጽኑ መሆን እንደሚችሉ ለልጆቹ ያስተምራል።

  • የሁሉም የቤተሰቡ አባላት ህይወት ጥራት መሻሻል። ተሳትፎ የሚያደርጉ (ወይም ልጆችን በመንከባከብ ውስጥ መልሰው ለመሳተፍ የሚታገሉ) አባቶች የኢኮኖሚ ድህነት ቢኖርባቸውም እንኳን ጠንካራ የኩራት እና በራስ የመተማመን ስሜትን ያዳብራሉ። ይህም የልጆቻቸውን ዕድገት የተሻለ ያደርገዋል። በተለይም ደግሞ ወጣት ወንዶች የአርአያነትን ሚና ከሚጫወት አባት ከሚያገኙት ትኩረት እና ምክር ተጠቃሚ ይሆናሉ። ወጣት ሴቶችም እንዲሁ ቤተዘመዱ ውስጥ ያሉ ሌሎች ወንዶች የአባትን ሚና የሚጫወቱ ከሆነ የተሻለ ጥበቃ ያገኛሉ።

እነዚህ የጥናት ውጤቶች በማህበረሰቡ ውስጥ በምትሰሩት ሥራ ውስጥ የምታስተላልፏቸው መሰረታዊ መልዕክቶች ናቸው። ነገር ግን የምትጋፈጡት ህጻናትን ከመንከባከብ ጋር በተያያዘ ኃላፊነት የሚከፋፈልበትን መንገድ የሚመለከቱ የቆዩ ባህላዊ ሀሳቦችን ነው (ተጨባጭ እና ስነ-ልቦናዊ እንክብካቤ ማድረግ ያለባቸው ሴቶች ብቻ ናቸው የሚለውን ማለት ነው)። በዘመናዊ ማህበረሰቦች በከተሞች ውስጥ እናቶች እና አባቶች እነዚህን ኃላፊነቶች መጋራት እየጀመሩ ነው፤ ይህም የህጻናትን ዕድገት በከፍተኛ ሁኔታ የሚያሻሽል ነው። በተጨማሪም ባህላዊ ዕሴቶች ከላይ ከተጠቀሱት የአባት ተሳትፎ የሚያካትታቸው ነገሮች ጋር በደንብ በማይጣጣሙ መንገዶች ወንድነትን እና አባትነትን ይተረጉማሉ። ምንም እንኳን የሚያሳምሙ ቢሆኑም ለውጥ እንዲመጣ እነዚህ አመለካከቶች እና አሉታዊ ተሞክሮዎች (በማህበረሰቡ ውስጥ እንዲሁም በእናቶች እና በአባቶች መካከል) የግድ በግልጽ መውጣት አለባቸው።

በማህበረሰቡ ትስስር ውስጥ በአባቶች ላይ ትኩረት መፍጠር

አሁን ደግሞ እንዴት ቁልፍ የማህበረሰብ ባለድርሻ አካላትን ማነጋገር እና የማህበረሰብ ስብሰባዎቻችሁን ማቀድ እንደምትችሉ እንመልከት። በጥናታችን እና በቃለ መጠይቆቻችን ውስጥ ማናቸውም ጠንካራ ማህበራዊ ቡድኖች ለአባቶች ተሳትፎ ወሳኝ መሆናቸው ግልጽ ነው። እነዚህ ቡድኖች በማህበረሰቡ ውስጥ ያሉ ጎረቤቶች፣ የክርስቲያን ወይም የሙስሊም ሀይማኖታዊ ቡድኖች፣ በኤስ ኦ ኤስ መንደሮች ወይም በሌሎች መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ሠራተኞች የተቀቋቋሙ ቡድኖች፣ በማህበረሰቡ ውስጥ እንዳሉ የእግር ኳስ ቡድኖች ያሉ ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎች፣ ወዘተ ሊሆኑ ይችላሉ። ዋናው ግብ ለአባቶች የእኔ ነው የሚሉትን እና ስነ-ልቦናዊ እና ማህበራዊ ድጋፍ የሚያገኙበትን ቦታ መስጠት ነው። ይህም ሀዘኑ የሚፈጥረውን ስቃይ በዕጾች፣ አልኮልን ያለአግባብ በመጠቀም እና ራስን ምስኪን አድርጎ በማየት ለማከም የሚሞክሩ አሉታዊ ቡድኖችን እንዲተው ይረዳቸዋል። በተጨማሪም በእነዚህ ቡድኖች ውስጥ ያሉትን አሉታዊ ባህላዊ እሴቶች (በትዳር ውስጥ ኃይልን መጠቀምን፣ ወንድ የበላይ ነው የሚሉ አመለካከቶችን፣ የወሲብ ጥቃትን፣ ወዘተ የሚፈቅዱ) ለማስወገድ ይረዳቸዋል።