ክፍለ ጊዜ 7/21

ገጽ 4/5 ርዕስ ለ፡- 3-18 ዓመት ዕድሜ

ርዕስ ለ፡- 3-18 ዓመት ዕድሜ

ዕድሜአቸው ሦስት ዓመት እና ከዚያ በላይ የሆኑ ህጻናት ለመለያየት የሚሰጡት ምላሽ
ዕድሜአቸው ሦስት ዓመት እና ኪያ በላይ የሆኑ ህጻናት እንደ የተፈጥሮ ወላጆቻቸው ካሉ ሰዎች ጋር አስቀድሞ የነበረ ቅርበት ይኖራቸዋል። አንድ ህጻን ከትንሽ ዕድሜው ጀምሮ በእናንተ እንክብካቤ ውስጥ ከነበረ ህጻናት ከወላጆቻቸው ጋር በጣም በሚቀራረቡበት በመደበኛው መልኩ ከእናንተ ጋር በጣም የመቀራረብ ዕድሉ ሰፊ ነው።

ዕድሜአቸው ከሦስት ዓመት በላይ የሆነ ህጻናት (ተመድበው በእንክብካቤ ላይ በሚሆኑበት ውቅት) ስለራሳቸው እና ስላሳለፏቸው ከባድ መለያየቶች ይበልጥ የተሻለ ግንዛቤ ይኖራቸዋል። አስቀድመው ከወላጆቻቸው ወይም ከሌሎች ሰዎች ጋር ከፍተኛ ቅርበት ይኖራቸዋል፤ ስለዚህ ችላ መባልን ያሳለፉ ከሆነ የፈጠረባቸው በአንጻሩ ዘላቂ የሆኑ ችግሮች ሊኖሩ ይችላሉ። ህጸኑ ከባድ መለያየቶችን (ወይም ለረጅም ጊዜ የቆዩ መለያየቶችን) ያሳለፈ ከሆነ የሀዘን እና የማገገም ሂደቱ ምን ዓይነት እንደሚሆን የሚወስነው ህጻኑ ስላሳለፈው ነገር በግልጽ ለማውራት እንክብካቤ ሰጪዎቹ ያላቸው ፈቃደኝነት ነው።

ሰውን ማጣት ከስሜት አንጻር ያለው ትርጉም፡- ዝቅተኛ ግምት ለራስ መስጠት
ህጻናት ለከባድ ወይም በጣም ረጅም ጊዜ ለሚቆዩ መለያየቶች በመደበኛ መልኩ ምላሽ የሚሰጡት ከስሜት አንጻር በመተርጎም ነው፡-“ትተውኝ ሄደዋል፤ ስለዚህ የማልወደድ እና ዋጋ ቢስ ሰው ብሆን ነው”። ይህ አተረጓጎም ስሜታዊ እንደሆነ እና ከእንክብካቤ ሰጪዎች ከተሰጧቸው ምክንያታዊ ማብራሪያዎች ጋር ብዙም ግንኙነት እንደሌለው መገንዘብ አስፈላጊ ነው (ህጻኑ “ከሚያውቀው” ነገር ይልቅ የሚሰማው ስሜት ነው)። ህጻኑ በእንክብካቤ ሰጪዎቹ የተሰጡትን ምክንያታዊ ማብራሪያዎች በሙሉ ደግሞ ማለትን ለምዶ ሊሆን ይችላል፤ ነገር ግን እንዲያም ሆኖ ስሜቱ ላይጠፋ ይችላል እንዲሁም ህጻኑ ካለማቋረጥ በማንነቱ ሀፍረት ሊሰማው እና ህይወቱ ትርጉም ሊያጣበት ይችላል።
የዋጋቢስነት ስሜትን ለመከላከል ጥቅም ላይ የሚውሉ ብስለት የጎደላቸው ዘዴዎች

አንዳንድ ህጻናት ሁኔታውን የሚቋቋሙት ወላጆቻቸው ወይም የተለዩአቸው ሌሎች ሰዎች ላይ በመናደድ ወይም እነሱን በመጥላት ነው። ይህም እነሱን የመናፈቅን ስቃይ ያስቀርላቸዋል።

አንዳንድ ህጻናት “ገዳም እንደገባ ሰው” ይሆናሉ፡- ኮምፒዩተራቸውን ወይም አሻንጉሊቶቻቸውን ይዘው ክፍላቸው ውስጥ ከሰው ተነጥለው በመቀመጥ አልወጣም እንዲሁም ጓደኞቼን አልጠራም ይላሉ። ማናቸውንም ማህበራዊ ዝግጅቶች ወይም ግብዣዎች የሚጠሉ በመሆኑ ምክንያት ፈልገው እምቢ ይላሉ። ከዚህ ጀርባ ያለው ከስሜት ጋር የተያያዘ ሀሳብ “ጓደኞች ካላፈራሁ ወይም ከሰው ጋር ካልተግባባሁ ማንም ሰው እንደገና ትቶኝ ሊሄድ አይችልም” ነው።

ማንኛውም ህጻን ይህን ስሜት መቋቋም አይችልም፤ ስለዚህ ህጻናት ዋጋቢስነት እና ያለመፈለግ ስሜት እንዳይሰማቸው ስነ-ልቦናዊ መከላከያ ዘዴዎችን ያበጃሉ። ምንም እንኳን እነዚህ ምላሾች ችግር ያለባቸው ቢመስሉም ፍጹም ምክንያታዊ ናቸው፡- ህጻኑ እንደገና ሰውን ማጣት እንዳይደርስበት ራሱን መከላከያ ዘዴ ይፈልጋል። ህጻናት ብስለት ስለሌላቸው ስቃይን ለመከላከል የሚጠቀሟቸው ዘዴዎች በጣም ያልበሰሉ ሊሆኑ ይችላሉ። ነገር ግን ህጻኑ ሀዘንን እና ድባቴን ለመከላከል በሠዓቱ ሊያገኝ የቻለው ምርጥ መፍትሄ እንደሆነ ማስታወስ አለባችሁ። እነዚህን ምላሾች በሁሉም ህጻን ላይ ልታዩአቸው ትችላላችሁ፤ ነገር ግን ከባድ መለያየትን ባሳለፉ ህጻናት ላይ ይበልጥ በጣም ጠንካራ እና አንዳንድ ጊዜም ጎጂ በሆነ መልኩ ይስተዋላሉ እንዲሁም ለጨዋታ እና ለመማር ጥቅም ላይ ሊውል የሚገባውን ጉልበት በሙሉ የሚወስዱ ናቸው።

 

  • አንዳንድ ህጻናት ይህ ስሜት እንዳይሰማቸው ለመከላከል ስላሳለፉት ህይወት ለማውራት ከነጭራሹ ፈቃደኛ አይሆኑም።
  • አንዳንድ ህጻናት “የውሸት ጨለምተኝነት” ያሳያሉ፡- ምንም ነገር ቢፈጠር የተረጋጉ ይመስላሉ እንዲሁም ከሌሎች ሰዎች ጋር እንዲቀራረቡ ግብዣዎች ሲቀርቡላቸው ሁል ጊዜም “ስለእናንተ ወይም ስለጓደኞቻችሁ ወይም ስለ ሌላ ማንኛውም ሰው ግድ አይሰጠኝም። ለምንም ነገር ቦታ አልሰጥም፤ ተውኝ!” የሚል ደስ የማይል አቋም ይይዛሉ (በክፍለ ጊዜ 9 ውስጥ ያለውን የመሸሽ የአቀራረብ ዘዴ ተመልከቱ)። ይህን አቋም ለመረዳት አይከብድም ምክንያቱም ህጻኑን ሰው ማጣት እንደአዲስ እንዳይደርስበት ይጠብቀዋል እንዲሁም ሌሎች ሰዎችን ያርቃል (እነሱን ማጣት የሚያመጣው ለውጥ አይኖርም)።
  • አንዳንድ ህጻናት ሌላ ሰው ላይ በጣም ጥገኛ ይሆናሉ እንዲሁም ሁል ጊዜም “ጥሩ ልጅ” ይሆናሉ፤ ሙሉ ሀይላቸውንም ከእንክብካቤ ሰጪዎቻቸው ጋር በመስማማት ያጠፋሉ። ማንኛውም ግጭት እንዳይፈጠር ለመከላከል ጥረት ያደርጋሉ እንዲሁም ስለማንኛውም ነገር የራሳቸውን አቋም ላለመያዝ ወይም ከእንክብካቤ ሰጪዎቻቸው ጋር ያለመስማማት ውስጥ ላለመግባት ይወስናሉ (“ምን ማድረግ እንዳለብኝ ንገሩኝ፤ እኔ ምንም አላውቅም” ዓይነት)። አብዛኛውን ጊዜ ሌሎች ሰዎች ከሚጠብቁት ነገር ጋር የሚጋጭ ሊሆን ስለሚችል ውሳኔዎችን ለመወሰን ይፈራሉ።
  • አንዳንድ ህጻናት “ሁሉም ነገር ፍጹም ትክክል መሆን አለበት” የሚሉ ሰዎች ይሆናሉ፡- ካለማቋረጥ ማንኛውንም ነገር ከሚገባው በላይ ለማድረግ ጥረት ያደርጋሉ እንዲሁም ነገሮችን በትክክል መሥራታቸውን በማጣራት ላይ ያተኩራሉ። ትናንሽ ስህተቶችንም እንኳን መሥራት ወይም ነገሮችን በሙሉ አቅማቸው ያለመፈጸም በጣም ያስፈራቸዋል። ማንኛውም ተራ ችግር ሲያጋጥማቸው ወይም ስህተት ሲሰሩ በጣም ጭንቀት ይፈጥርባቸዋል (“ምንም ባደርግ እሳሳታለሁ፣ የማይሳካለት ሰው ነኝ፣ ምንም ያህል ጠንክሬ ብሞክር ምንም ነገር ላይ ጎበዝ አይደለሁም። ደደብ ነኝ፤ መሞት ነው የምፈልገው፣ ወዘተ”)።
  •  አንዳንድ ህጻናት ካለማቋረጥ ይቅበጠበጣሉ እንዲሁም ይጨነቃሉ እንዲሁም ከሞላ ጎደል ቀዥቃዣ ይሆናሉ። ተረጋግተው መቀመጥ ስለማይችሉ ፈጽሞ አያርፉም፤ እንዲሁም በጣም በተጣደፈ መልኩ ካለማቋረጥ ሊያወሩ ይችላሉ፤ ይህም ህጻኑ በኃይል የተሞላ ህጻን ብቻ ሳይሆን ለአፍታ እንኳን የማያርፍ እና ያለፈውን ጊዜ ላለማስታወስ ጥረት እንደሚያደርግ የሚያሳይ ነው።
  •  አንዳንድ ህጻናት “ገዳም እንደገባ ሰው” ይሆናሉ፡- ኮምፒዩተራቸውን ወይም አሻንጉሊቶቻቸውን ይዘው ክፍላቸው ውስጥ ከሰው ተነጥለው በመቀመጥ አልወጣም እንዲሁም ጓደኞቼን አልጠራም ይላሉ። ማናቸውንም ማህበራዊ ዝግጅቶች ወይም ግብዣዎች የሚጠሉ በመሆኑ ምክንያት ፈልገው እምቢ ይላሉ። ከዚህ ጀርባ ያለው ከስሜት ጋር የተያያዘ ሀሳብ “ጓደኞች ካላፈራሁ ወይም ከሰው ጋር ካልተግባባሁ ማንም ሰው እንደገና ትቶኝ ሊሄድ አይችልም” ነው።
  • አንዳንድ ህጻናት ሁኔታውን የሚቋቋሙት ወላጆቻቸው ወይም የተለዩአቸው ሌሎች ሰዎች ላይ በመናደድ ወይም እነሱን በመጥላት ነው። ይህም እነሱን የመናፈቅን ስቃይ ያስቀርላቸዋል።
ግልጽ ውይይት ማድረግ ሰውን ማጣትን እንዲረዱ እና እንዲቋቋሙ ህጻናትን ይረዳቸዋል፡- ለግልጽ ውይይት ምቹ የሆነ ሁኔታን መፍጠር
ከእንክብካቤ ሰጪዎች ጋር ግልጽ ውይይት ማድረግ አስፈላጊ እንደሆነ ከሰው ጋር ለመለያየት በሚሰጡ ምላሾች ላይ የተሰራው ጥናት ያሳያል፡-አንድ ህጻን ከመለያየት ጋር ስለተያያዙ ተሞክሮዎች በሚያወራበት ወይም በሚያስተናግድበት በማንኛውም ጊዜ ካሳለፈው ነገር ምንነት ጋር በተያያዘ ያሉት ስሜቶች እና ሀሳቦች ምን እንደሆኑ ያውቃል። እያንዳንዱ ጊዜ ላይ ሰውን የማጣቱ ስሜት ጥንካሬው እየቀነሰ ይመጣል እንዲሁም ትውስታዎቹ እና ግንዛቤዎቹ ይበልጥ መስመር እየያዙ ይመጣሉ። ህጻኑ ከሌሎች ህጻናት ጋር ተመሳሳይ የሆነ ደረጃ ላይ እስኪደርስ እና የአእምሮ ሁኔታውን እና የመጫወት፣ የማሰስ እና የመማር ፍላጎቱን የማይረብሽ ተፈጥሮአዊ የሆነ ሀዘን ሊሰማው እስከሚችል ድረስ ማለት ነው። የምትሠሩት ሥራ ዓላማው ሀዘኑን በሙሉ ማስወገድ ሳይሆን የሚሰማው ስሜት ጥንካሬው እና ዝብርቅርቅነቱ እንዲቀንስ ለህጻኑ እገዛ ማድረግ ነው።

እንክብካቤ ሰጪዎች ከዚህ በፊት ህጻኑ ያሳለፈውን ሰውን የማጣት ተሞክሮ ካስተባበሉ፣ ችላ ካሉ ወይም ካቃለሉ ህጻናት የራሳቸውን ምላሽ የሚያስተናግዱበትን መንገድ እንደማያሻሽሉ እና ይህም ለሰብዕናቸው ዕድገት ጎጂ ሊሆን እንደሚችል ጥናቶች ያሳያሉ። ለምሳሌ፡- በቀደመው ጊዜ ህጻናት ጉዲፈቻ ወይም የአደራ ቤተሰብ እንክብካቤ ላይ በሚሆኑበት ወቅት በጣም አሳፋሪ እና ከማህበራዊ ደንቡ ውጭ ነበር። ይህ ህጻናቱን የመገለል ስሜት እንዲሰማቸው አድርጓቸዋል እንዲሁም ይህን ለመረዳት የሚችሉበት ዕድሜ ላይ ሲደርሱ “ራሳቸውን መሆን ይፈቀድላቸው እንዳልነበር” ሲያስታውሱ በጣም ያስደነግጣቸዋል። በዚህም የተነሳ በርካታ ህጻናት በከፍተኛ ሰቆቃ ውስጥ ያለፉ እና በጣም መጥፎ ህይወት የነበራቸው ናቸው። በቀደመው ህይወታቸው የጉዲፈቻ ወይም የአደራ ቤተሰብ ልጆች ከነበሩ ልጆች ጋር በሚደረጉ ቃለ መጠይቆች ውስጥ አብዛኛውን ጊዜ ከሚገለጹ ቅሬታዎች ውስጥ አንዱ የሚከተለው ነው፡- “በጣም ዋና ስለሆነው ጉዳይ (ወላጆቼን ስለማጣቴ) አዋርቶኝ የሚያውቅ ሰው የለም”።

ስለሆነም የሞያዊ ሥራችሁ ህጻኑ ስላሳለፈው ነገር ለመወያየት ነጻነት እና የመጋበዝ ስሜት እንዲሰማው የሚያደርግ ሁኔታን ለመፍጠር መሥራት ነው። ይህንንም በበርካታ የተለያዩ እንቅስቃሴዎች አማካኝነት ማከናወን ይቻላል።

ከህጻኑ ጋር ሰውን ስለማጣት እንዴት እና መቼ እንደምታወሩ መወሰን አለባችሁ። አብዛኛውን ጊዜ የቤት ውስጥ ሥራ በማከናወን ላይ እያላችሁ ብታደርጉት ጥሩ ነው (ለምሳሌ ህጻኑ ጠረጴዛ ጋር ተቀምጦ ስዕል እየሳለ ወይም የቤት ሥራውን እየሠራ እናንተ ደግሞ ምግብ እያዘጋጃችሁ እያለ ወይም ከእንቅልፍ ሠዓት በፊት ወሬ እንደምታወሩበት ጊዜ ያለ ሌላ መደበኛ የዕለት ተዕለት ሁኔታ ላይ)። እነዚህ ሁኔታዎች ውይይት ለማድረግ ጥሩ አጋጣሚዎች ሊሆኑ ይችላሉ። ትዕግሰተኛ ሁኑ፤ ይህ የውይይት ሂደት ሳምንታት ወይም ዓመታት ሊወስድ ይችላል። ህጻኑ አዲስ የብስለት ወይም የዕድገት ደረጃ ላይ በደረሰ ቁጥር በዚህ ጉዳይ ላይ እንደገና መወያየት እና አዲስ ዕይታዎችን ማግኘት ሊኖርበት ይችላል።

ታንዛኒያ፣ አሩሻ ውስጥ የሚገኝ የኤስ ኦ ኤስ የህጻናት መንደር ውስጥ የሚኖረው ፒተር ያለበትን ይህን ቪዲዮ ተመልከቱ። ፒተር አማራጭ የሕጻናት እንክብካቤ ውስጥ ስለማደግ እና እንክብካቤ ሰጪው እንዴት ለዕድገቱ እና ለደህንነቱ ከፍተኛ ድጋፍ ታደርግለት እንደነበረ እና እያደረገችለት እንደሆነ ያወራል።

የራሱ ምላሾች ጤናማ መሆናቸውን እንዲገነዘብ ህጻኑን መርዳት
  • ከዚህ በላይ ባለው እና “የዋጋቢስነት ስሜትን ለመከላከል ጥቅም ላይ የሚውሉ ብስለት የጎደላቸው ዘዴዎች” የሚለው አንቀጽ ውስጥ ያለውን ዝርዝር ተመልከቱ።
  • እናንተ በምትንከባከቡት ህጻን ላይ አብዛኛውን ጊዜ የምታዩት የተጣለ የመሆን ስሜትን መከላከያ ዘዴ የትኛው እንደሆነ አጣሩ። እናንተም ህጻኑም ጥሩ ስሜት ውስጥ ስትሆኑ እና ጊዜ ሲኖራችሁ ህጻናት ትልቅ ቦታ የሚሰጧቸውን ሰዎች (እናታቸውን፣ አባታቸውን፣ እህት ወንድሞቻቸውን ወይም ይወዷቸው የነበሩ የቤት እንስሳትን) ሲያጡ ምላሽ ስለሚሰጡበት መንገድ ልታነጋግሩት እንደምትፈልጉ ለህጻኑ ንገሩት።
  • ህጻን ልጃችሁ ሰጥቷል ብላችሁ የምታስቡትን ምላሽ ግለጹ እና በርካታ ህጻናት ትልቅ ቦታ የሚሰጡትን ሰው ሲያጡ የሚያደርጉት ነገር እንደሆነ ንገሩት። ለምሳሌ፡-“አንዳንድ ጊዜ ህጻናት የሚወዱትን ሰው ያጡ ይሆኑ እና እንደገና ሌላ ሰው እንዳያጡ ሊፈሩ ይችላሉ። ስለዚህ ሌሎች ሰዎችን ለማናገር ፈቃደኛ አይሆኑም እንዲሁም ቀኑን ሙሉ ከክፍላቸው አይወጡም። በርካታ ህጻናት የሚያደርጉት እንደዚያ ነው፤ እኔም በጣም ይገባኛል። ምክንያቱም ክፍላቸው ውስጥ ብቻቸውን ሆነው ከቆዩ እና ከማንም ሰው ጋር ጓደኛ ካልሆኑ እንደገና የማይፈለግ ሰው የመሆን ስሜት አይሰማቸውም። ይሄ በጣም ይገባኛል!
  • ወይም ደግሞ ለህጻኑ ከልጅነት ህይወታችሁ የተወሰደ ተመሳሳይ ታሪክ ልትነግሩት ትችላላችሁ፡-“የአንተ ዕድሜ ላይ እያለሁ እናቴ እና አባቴ በጣም ሥራ ይበዛባቸው ስለነበረ አብዛኛውን ጊዜ ብቻዬን እሆን ነበር። ከሌሎች ህጻናት ጋር ጓደኛ ለመሆን ስሞክር አብዛኛውን ጊዜ አይፈልጉኝም ነበር እና ይተባበሩብኝ ነበር። ስለዚህ ቀኑን ሙሉ ክፍሌ ውስጥ ለመቀመጥ ወሰንኩኝ፤ እንደማይወዱኝ እና እንደማይፈልጉኝ እርግጠኛ ስለነበርኩኝ ሌሎች ሰዎችን ማነጋገር አልፈልግም ነበር። ካደግኩኝ በኋላ ግን ብዙ ህጻናት እንደዚህ እንደሚያደርጉ አወቅኩኝ፤ እና ብልህነት ነው ብዬ አስባለሁ ምክንያቱም እንደገና የማይፈለጉ ሰዎች እንዳይሆኑ ይከላከልላቸዋል”።
  • ለህጻኑ ስለአንድ የተተወ ህጻን የእንቅልፍ ሰዓት ላይ የሚነገር ተረት ተረት ልትፈጥሩለት ወይም ልታነቡለት ትችላላችሁ – እንደ ኦሊቨር ትዊስት (ወይም ህጻኑ ሊያውቀው የሚችል የእናንተ ሀገር ልብ ወለድ ውስጥ ያለ ሌላ ሰው) ያለ። እግረ መንገዳችሁን ተረቱ ውስጥ ያለው ሰው የሚሰማው ስሜት ወይም የሚያስበው ነገር ምን እንደሆነ ያውቅ እንደሆነ ህጻኑን ልትጠይቁት ትችላላችሁ።
  • አሻንጉሊቶችን፣ ስዕሎችን ወይም ሸክላ በመጠቀም ከህጻኑ ጋር መጫወት ትችላላችሁ። የማይፈለግ መሆን ወይም ወላጆቹን ማጣት ደርሶበት ሁኔታውን መቋቋም የሚችልባቸው መንገዶችን የሚያገኝ አንድ ህጻንን የሚመለከቱ ተረቶችን መጠቀምም እንዲሁ።
  • ተለቅ ላሉ ህጻናት እና የአሥራዎቹ ዕድሜ ውስጥ ለሚገኙ ልጆች፡- ለህጻኑ ሞባይል ስልክ (ወይም ቪዲዮ መቅረጽ የሚችል ካሜራ) ልትሰጡት እና ወላጆቹን ወይም ሌሎች ሰዎችን ለማጣት ምላሽ ስለሰጠበት መንገድ አጭር ፊልም ወይም ቃለ መጠይቅ እንዲሠራ ልትረዱት ትችላላችሁ። ኢንተርኔት ያላችሁ ከሆነ የአደራ ቤተሰብ እንክብካቤ ላይ ካሉ ሌሎች ታዳጊዎች ጋር እንዲገናኝ እና በፌስቡክ ወይም ሌላ ሚዲያ አማካኝነት እንዲያነጋግራቸው ታዳጊውን ልትረዱት ትላላችሁ።
  • ከህጻኑ መምህር ጋር ጥሩ ግንኙነት ያላችሁ ከሆነ፡- “የሚወዱትን ሰው ወይም ነገር ማጣት” የሚል ጭብጥ ያለው የአንድ ቀን ወይም የአንድ ሳምንት ዝግጅት እንዲያዘጋጅ መምህሩን ጠይቁት። በመምህሩ ድጋፍ ህጻናቱ ስዕሎችን፣ ቴአትርን፣ ወዘተ በመጠቀም ለምሳሌ እንደ አያት ወይም ሌላ ሰው ወይም ነገር ያሉ ያጧቸውን ነገሮች እንደ ምሳሌ ሊያቀርቡ ይችላሉ። ከዚያም ህጻኑ አንድን ሰው ስለማጣት ማውራት እንዲችል ማገዝ ሰለሚቻልበት መንገድ ከመምህሩ ጋር ልትወያዩ ትችላችሁ።
  • ከዚህ ጽሁፍ ያገኛችሁትን ተነሳሽነት መሠረት በማድረግ ከእነዚህ አማራጮች ውስጥ አንደኛውን እንዴት፣ መቼ እና የት እንደምትጠቀሙት ወይም አዲስ አማራጭ እንደምትቀርጹ ጻፉ። ዕቅዳችሁን ሥራ ላይ ካዋላችሁ በኋላ ማታወሻዎችን ጻፉ፡- እንዴት ነበር፣ ህጻኑ ምን ዓይነት ምላሽ ሰጠ፣ ለእናንተ የከበዳችሁ ምን ነበር፣ ከመሞከር ያገኛችሁት ትምህርት ምንድን ነው፣ እንዴት ትቀጥላላችሁ?
ህጻኑ ለሚሰጠው ምላሽ ዕውቅና ስጡ እንዲሁም የሚሰጠውን ምላሽ ጠብቁ
አሁን ሰው ስለማጣት በግልጽ ውይይት ለማድረግ የሚያስችል ሁኔታን ፈጥራችኋል። ስለዚህ የራሱ ክፍል ውስጥ ቀኑን ሙሉ መዋል ጥሩ እንዳልሆነ ለህጻኑ አትንገሩት ወይም ለህጻኑ ምክር መስጠት አትጀምሩ፤ ዝም ብላችሁ አዳምጡ እንዲሁም ህጻኑ ማውራት የሚፈልግ ከሆነ እንዲያወራ ፍቀዱለት። ምን አልባት ህጻኑ ወዳላችሁት ነገር ተመልሶ እስኪመጣ አንድ ወይም ሁለት ቀን ይወስድ ይሆናል። ህጻኑ ማውራት ከጀመረ ራሳችሁን በአዎንታ እየነቀነቃችሁ ተመስጣችሁ አዳምጡ እና ስለሚያስበው እና ስለሚሰማው ነገር ህጻኑን አድንቁት።

ምን አልባትም መጀመሪያ ላይ ለረጅም ጊዜ ማድረግ የሚያስፈልጋችሁ የሚከተለውን ሊሆን ይችላል፡- ቀለል ባለ መልኩ ሰውን ስለማጣት በማውራት እና ሀሳባችሁን ለማካፈል እና ለማዳመጥ ፈቃደኛ መሆናችሁን በማሳየት ህጻኑን እንዲያገግም መርዳት።

ህጻኑ የሚጠቀመው ዘዴ ያሉትን ጥቅሞች እና ጉዳቶች ማስረዳት
ህጻኑ በትዕግስት እንዳዳመጣችሁት እና ምላሹን እንደተረዳችሁት እንደሚሰማው እርግጠኛ ስትሆኑ ህጻኑ የሚጠቀመው ዘዴ ስላሉት ጥቅሞች እና ጉዳቶች ውይይት መጀመር ትችላላችሁ።

ለምሳሌ፡-
ቀኑን ሙሉ ክፍሌ ውስጥ ቁጭ ብዬ ስዕል በመሳሌ እንዲያውም ሳድግ ጎበዝ ሰዓሊ ሆንኩኝ። ይህ በጎ ጎኑ ነበር። ነገር ግን ወጥቼ ሌሎች ጓደኞችን ለማፍራት ድፍረቱ ስላልነበረኝ ከዚህ በተጨማሪ በጣም በጣም ብቸኛ ነበርኩኝ። የማልፈለግ ወይም ማላገጫ መሆንን እፈራ ስለነበር እንደዚያ ለማድረግ ባሰብኩኝ ቁጥር በሩን ልከፍት እልና እመለስ ነበር። ስለዚህ መጥፎ ጎኑ አብሬው የምጫወተው ሰው ያልነበረኝ መሆኑ እና ት/ቤት ውስጥ ጓደኛዬ እንዲሆኑ ሌሎች ልጆችን ያለመጠየቄ ነው – ይህን ስሜት ታውቂዋለሽ?

ይህን በምታደርጉበት ጊዜ ዘዴው በተጨባጭ ለጊዜው ፍርሀትን የሚያስወግድ ቢሆንም ለዘላቂው ብቸኛ እንደሚያደርግ ቀለል ባለ መልኩ ለህጻኗ ታሳዩአታላችሁ። ከዚያ ህጻናት እንዴት እንደገና የማይፈለግ ሰው መሆንን ወይም የሚወዱትን ሰው ማጣትን እንደሚፈሩ ማውራት ትችላላችሁ።

አማራጭ የመቋቋሚያ መንገዶችን ጠቁሙ
ቀጣዩ እርምጃ ህጻኑ እንደገና ሰውን የማጣት ወይም እንደገና የማይፈለግ ሰው የመሆን ፍርሀትን መቋቋሚያ ሌሎች መንገዶችን እንዲያስብ ማድረግ ነው። ለምሳሌ፡- “አንድ ቀን ክፍሌ ውስጥ ብቻዬን ከቆየሁ እስከመጨረሻው ብቸኛ እንደምሆን ገባኝ። ጓደኛዬ እንዲሆን የሆነ ሰውን ከጠየቅኩኝ እምቢ ይሉኛል ብዬ በጣም እፈራ ነበር። ነገር ግን አክስቴ ጓደኛ ከፈለግሽ ምን አልባት ስምንት ሰዎች እምቢ ይሉሽ እና ሁለት ሰዎች እሺ ይሉሽ ይሆናል፤ እና እነዚህ እሺ የሚሉሽ ሁለት ሰዎች ግን በኋላ ላይ የቅርብ ጓደኞችሽ ሊሆኑ ይችላሉ አለችኝ። አክስቴ ሌሎች ሰዎች ቢንከባከቡኝ ምንም ችግር እንደሌለው እና የሚያሳፍር የሚሆንበት ምንም ምክንያት እንደሌለ ነገረችኝ። እንዲያውም በሺዎች የሚቆጠሩ ህጻናት የሚኖሩት ያለወላጅ ነው። ስለዚህ ከትምህርት በኋላ መጥተው አብረውኝ እንዲጫወቱ የክፍሌን ልጆች መጋበዝ ጀመርኩኝ፤ አክስቴም እንዳናግራቸው አገዘችኝ። አብዛኛዎቹ እምቢ ነበር ያሉኝ፤ ነገር ግን አንደኛዋ እሺ አለችኝ። ከዚያ በኋላ ለብዙ ዓመታት የቅርብ ጓደኞች ሆንን። ምን አልባት አንቺም የሆነ ቀን ፍርሀትሽን ለማሸነፍ ጥንካሬውን አግኝተሸ ሌሎች ልጆችን መጋበዝ ትጀምሪ ይሆናል።”

ወይም፡- “ብቸኝነት ሲሰማሽ በጣም ትናደጃለሽ፣ ከዚያ መጨቃጨቅ ትጀምሪአለሽ፣ ከዚያ የባሰ ሀዘን እና የማትረቢ ሰው እንደሆንሽ ይሰማሻል። ምን አልባት በሚቀጥለው ጊዜ ንዴት ሲሰማሽ ብቸኝነት ተሰምቶኛል ለማለት መሞከር የምትችይ ይመስልሻል?”