ክፍለ ጊዜ 13/21

ገጽ 4/5 ርዕስ ለ፡- ከህጻኑ ወላጆች ጋር ግንኙነትን መመስረትን መለማመድ የሚቻልበት መንገድ – ግንኙነቶች እና አሠራሮች

ርዕስ ለ፡- ከህጻኑ ወላጆች ጋር ግንኙነትን መመስረትን መለማመድ የሚቻልበት መንገድ – ግንኙነቶች እና አሠራሮች s

ከህጻኑ ወላጆች ጋር የሚኖረው ግንኙነት ሁለት ክፍሎች አሉት፡- ማህበራዊ ግንኙነቶችን መምራት እና ተጨባጭ አሠራሮች። ከተፈጥሮ ወላጆቹ ጋር መደበኛ የሆነ ግንኙነትን መምራት የምትችሉት እንዴት ነው? በጥቅሉ ከወላጆቹ ጋር በምታደርጓቸው ግንኙነቶች ውስጥ ሁሉ የሚከተለው አመለካከት ሊኖራችሁ እና ተግባራዊ ልታደርጉት ይገባል፡-

  • ሌላውን ሰው የመረዳት እና የመቀበል አመለካከት፡- “ልጃችሁን አሳልፋችሁ ለመስጠት መወሰናችሁን ወይም የነበረባችሁ መሆኑ ይገባኛል። በፍጹም አልወቅሳችሁም እንዲሁም ህጻኑን እኛ ጋር ማድረጋችሁ ኃላፊነት የተሞላበት ውሳኔ ነው፤ ህጻኑን እንድንንከባከበው ለእኛ ስለሰጣችሁንም ደስተኛ ነኝ። በተቻለን አቅም ሁሉ ከእናንተ ጋር መገናኘታችንን እንደምንቀጥል እና ተቀናጅተን እንደምንሰራ እርግጠኛ መሆን ትችላላችሁ።”
  • አስተማማኝ እንክብካቤ የሚያካትታቸውን አምስት ነገሮች ተጠቀሙ (ክፍለ ጊዜ 5ን ተመልከቱ)፡- መገመት የምትቻሉ ሁኑ፣ ስሜትን አገናዝቡ፣ የወላጆቹን ስሜት አንብቡ እና ያንን መሠረት በማድረግ እርምጃ ውሰዱ፣ ልታጽናኗቸው ዝግጁ ሁኑ፣ የወላጁን ስሜት ተጋሩ ነገር ግን እንደ ወላጁ አትሁኑ። ስለ ስሜቶች እና ፍላጎቶች አውሩ፤ ለምሳሌ፡- “አንዳንድ ጊዜ እንደምትቀኑ እና እንደምትቆጡን ይገባኛል። ራሳችሁ ልታደርጉት እየፈለጋችሁ ልጃችሁን ሌሎች ሰዎች ሲንከባከቡት ማየት ከባድ እንደሚሆን እርግጠኛ ነኝ። ሁሉም ወላጅ የሚያደርገው ነገር ነው፤ አንዳንድ ጊዜ በራሴ ልጅ የትምህርት ቤት አስተማሪ እቀናለሁ (እኛን ወላጆቹን ካለማቋረጥ እየተቸን ስለ እሷ ግን ሁል ጊዜም የሚያወራው ምን ያህል እንደሚወዳት ነው!”

  • በተለይም ደግሞ በእናንተ እንክብካቤ ስር ያለው ህጻን አጠገባችሁ በሚኖርበት ጊዜ፡- ስለ ወላጆቹ አዎንታዊ በሆነ መልኩ አውሩ እንዲሁም አዋሯቸው፡- “እናትህ ልታይህ እዚህ በመምጣቷ በጣም ደስ ብሎኛል፣ ድምጿ ሲያምር፣ ወዘተ”።
    • ልጃቸውን አሳልፈው መስጠት የነበረባቸው  ወላጆችን በተመለከተ አብዛኛውን ጊዜ እርስ በእርስ ይበልጥ መተዋወቅ እና ጓደኛሞች ጭምር መሆንም ትችላላችሁ እንዲሁም ልጃቸውን እንዲያድግ ማገዝ የሚለውን የጋራ ዓላማ በመያዝ ከወላጆቹ ጋር ህብረት ለመፍጠር መስራት አለባችሁ። ልጃቸውን የመንጠቅ ምንም ዓላማ የሌላችሁ መሆኑን ከመጀመሪያ ጀምሮ ልትነግሯቸው ይገባል።

    ከተጎዱ ወላጆች ጋር የሚደረጉ ጥየቃዎችን እና ግንኙነቶችን መምራት

    ከአደራ ቤተሰብ ህጻናቱ ጋር በተያያዙ ችግሮች የተነሳ ብቻ ሳይሆን ብዙ ጊዜ ከተጎዱ ወላጆች ጋር የሚኖረውን ግንኙነት ከመምራት ጋር በተያያዙ ችግሮች የተነሳ የሚፈርሱ አንዳንድ የአደራ ቤተሰብ ምደባዎች አሉ። ይህ ግንኙነት አንዳንድ ጊዜ ለአጠቃላይ የአደራ ቤተሰቡ የጭንቀት እና የግራ መጋባት ምንጭ ይሆናል።

    የተፈጥሮ ቤተሰቦቹ ለጥየቃ እንደመምጣት እና ሁለቱም ቤተሰቦች በአጠቃላይ እንደሚገናኙባቸው ሁኔታዎች ያሉ ግንኙነቶችን ለመምራት የሚረዱ አንዳንድ መርሆዎች እና ምክሮች እንደሚከተለው ቀርበዋል፡-

    1. “የወላጁ ወላጅ” ሁኑ፡-
    በጣም ብስለት የጎደላቸውን ወላጆች ምን አልባት ማየት ያለባችሁ እንደ ወላጆች ብቻ ሳይሆን ኃላፊነት በተሞላበት መልኩ ልጅን የማሳደጉ ስራ በጣም እንደከበዳቸው “ህጻናት” ጭምር ነው። ይህም ማለት የወላጆቹ የራሳቸው የልጅነት ዕድሜ በጣም አስጨናቂ የነበረ ከመሆኑ የተነሳ ሰዎቹ በጣም አልበሰሉም እንዲሁም ምን አልባትም ጥሩ ሁኔታ ውስጥ ሆነውም እንኳን በዕድሜ በጣም ከሚያንሷቸው ሰዎች እኩል ስሜታዊ እና ኃላፊነት የማይሰማቸው ሰዎች ሊሆኑ ይችላሉ ማለት ነው። አንደኛው ተጨባጭ ምክር የሚከተለው ነው፡- ማህበራዊ ክህሎቶቻቸውን በተመለከተ የወላጆቹን ዕድሜ በሦስት አካፍሉት።
    ይህን ስታደርጉ ወላጆቹን መቅረብ ያለባችሁ ወላጅነትን በተላበሰ መልኩ እንደሆነ፣ ለጥየቃ የሚመጡበትን ፕሮግራም ልታወጡላቸው እንደሚገባ፣ ትዕግስተኛ መሆን እንዳለባችሁ፣ ልጃቸውን እንደሚጠይቁ ቃል ገብተው ቢረሱት በእነሱ መናደድ እንደሌለባችሁ እና የሆነ ትንሽ ነገር ስላበሳጫቸው ቢጮሁባችሁ መረጋጋት እንዳለባችሁ ይገባችኋል።

    2. ማህበራዊ ሰራተኛውን ወይም የስራ መሪውን በመጠቀም የግንኙነት ማዕቀፍ አብጁ፡-
    በየስንት ጊዜው ጥየቃ ወይም ግንኙነት መደረግ እንዳለበት የሚወስኑት ባለሥልጣን አካላቱ ስለሆኑ ይህ የእናንተ ኃላፊነት አይደለም። ማዕቀፎቹ ለእናንተ ወይም ለህጻኑ እየሰሩ አይደለም ብላችሁ ካሰባችሁ ለባለስልጣን አካላቱ ማሳወቅ ትችላላችሁ። ወላጆቹ አታለዋችሁ የሚፈልጉትን ለማግኘት ከሞከሩ ወይም ስምምነት ከተደረገበት ጊዜ በላይ ለመገናኘት ጥያቄ ካቀረቡ ጭቅጭቅ አትጀምሩ። ይህ የሚወሰነው በእናንተ ሳይሆን በባለሥልጣን አካላቱ እንደሆነ እና የውል ማዕቀፎቹን መቀየር የሚችሉት ባለሥልጣን አካላቱ ብቻ እንደሆኑ ብቻ ግለጹላቸው።

    በተጎዱ ወላጆች ከሚደረጉ ጥየቃዎች ጋር የተያያዙ አንዳንድ ጠቅላላ ምክሮች
    በተጎዱ ወላጆች የሚደረጉ ጥየቃዎችን መምራትን የተመለከቱ 4 መርሆዎች፡-

    ሀ. ለመጀመሪያው ቀን ማዕቀፎችን ማስቀመጥ እና ጥብቅ መሆን፣ አመራር መስጠት፣ ሩህሩህ መሆን እና ግልጽ መሆን፡- “ወደ ቤታችን እንኳን ደህና መጣችሁ። ይህን ጥየቃ ጥሩ ተሞክሮ እንድታደርጉት አግዛችኋለሁ፤ ስለዚህ መጀመሪያ የምናደርገው ነገር ሁላችንም የምግብ ማብሰያ ክፍሉ ውስጥ እንቀመጥ እና እኔ ሻይ ሳፈላ እናንተ ደግሞ ተቀምጣችሁ ዘና ትላላችሁ።” ይህን በምታደርጉበት ወቅት ከመጀመሪያው ቅጽበት ጀምሮ አመራር እየሰጣችሁ መሆኑን ያሳያል፤ ይህም ወላጆቹ ከፈሩ፣ ከተናደዱ ወይም በጣም ያለመተማመን ስሜት ከተፈጠረባቸው አስፈላጊ ነው።

    ለ. በጥየቃው ወቅት ምን እንደሚከናወን የሚያሳይ የጊዜ ሰሌዳ አዘጋጁ እና ለሚደረጉት እንቅስቃሴዎች ተጨባጭ ዕቅድ አቅርቡ። ያለዕቅድ ዝም ብሎ “ቁጭ ብሎ ማውራት” ለሚሳተፉት ሰዎች በሙሉ በጣም አስጨናቂ ሊሆን ይችላል። ተጨባጭ የሆነ አንድ ነገር ላይ ማተኮር በአንጻሩ በጣም ቀላል ነው፡- “አሁን ደግሞ ቡና እየጠጣን ዛሬ ምን እንደምናደርግ እነግራችኋለሁ፡- በመጀመሪያ ከልጃችሁ ጋር መሳቅ እና ጥሩ ጊዜ ማሳለፍ እንድንችል በጋራ ኬክ እንጋግራለን። ከዚያ ትንሽ እረፍት ወስደን ሰፈሩ ውስጥ አጠር ያለ የእግር ጉዞ ልናደርግ ወይም ትንሽ ጨዋታ ልንጫወት እንችላለን። ከዚያ ህጻኑ እንዴት ነው ስለሚለው እንነጋገራለን፤ እንዲሁም የሰራቸውን ስዕሎች አሳያችኋለሁ። ከዚያ በኋላ ውጭ ላይ እንሰነባበት እና በሚቀጥለው ጊዜ እስከምትመጡ በጉጉት ይጠብቃችኋል። ከፈለጋችሁ እስከ እውቶብስ ፌርማታው ድረስ በእግሬ ልሸኛችሁ እችላለሁ።”

    ይህ ማለት አመራር በሚሰጥ መልኩ ማውራት እና ለወላጆቹ እንዴት እንደ ወላጅ እየሆናችኋቸው እንደሆነ በትህትና ማሳየት ማለት ነው፡- መተሳሰብ የሚታይባቸው እና ተጨባጭ እንክብካቤዎችን ማድረግ እና ምን ዓይነት ባህሪ እንዲያሳዩ እንደምትፈልጉ በዝርዝር ማሳየት። የተጎዱ ወላጆች መታለፍ የሌለባቸውን ተፈጥሮአዊ መስመሮች ከማወቅ አንጻር ችግሮች አሉባቸው፤ ስለዚህ ግንኙነትን በተመለከተ የምትሰጧቸው አመራር በጣም ግልጽ እና ቀላል መሆን አለበት። ለምሳሌ፡- “በስልክ ልታናግሩኝ የምትፈልጉ ከሆነ በየቀኑ (ከ    ሠዓት እስከ     ሠዓት) ልታገኙኝ ትችላላችሁ። ከዚህ ሠዓት ውጭ ብትደውሉልኝ ቤት ውስጥ ስራ በመስራት ላይ ወይም ህጻናቱን በመንከባከብ ላይ ስለምሆን ስልኬን አላነሳም።”

    ሐ. አጭር ጥየቃዎች አብዛኛውን ጊዜ ከረጅም ጥየቃዎች በላይ ስኬታማ ናቸው። ሁኔታው ጭንቀትን የሚፈጥር በመሆኑ የተጎዱ ወላጆች ራሳቸውን መቆጣጠር የሚችሉት ለተወሰነ ጊዜ ያህል ብቻ ነው። የ4 ሠዓታት ጥየቃ በሚያስቀይም ጭቅጭቅ ከተቋጨ በመቀጠል የአንድ ሠዓት ጥየቃዎችን ማድረግ እና የተሻለ ውጤታማ እንደሆነ ማየት ያስፈልጋል። የአደራ ቤተሰብ እንክብካቤያችሁን ለሚያስተዳድሩት ባለስልጣን አካላት ይህን ምክረ ሀሳብ ልትሰጧቸው ትችላላችሁ።

    መ. በጥየቃዎች ወቅት ለወላጆቹን ወላጅ ሁኑ። አብዛኛውን ጊዜ የተጎዱ እና ብስለት የሌላቸው ወላጆች ነገሮችን ማየት የሚችሉት ከራሳቸው አቅጣጫ ብቻ በመሆኑ ከልጃቸው ጋር የሚያደርጉት ግንኙነት ችግር ያለበት ነው ወይም የሚያወሩት ስለራሳቸው ፍላጎቶች ብቻ ነው። ወላጆቹ በጥየቃው ወቅት ሙሉውን ጊዜ ከህጻኑ ጋር መስተጋብር እንዲያደርጉ በመጠበቅ የተጎዳውን ጎናቸውን ማጋለጥ አያስፈልግም (ይህ ለእነሱ በጣም አስጨናቂ ሊሆን ይችላል)። ስለዚህ አንደኛው ጥየቃ ላይ ለምሳሌ የአደራ ቤተሰብ አባትየው ወላጆቹን ሲያዋራቸው የአደራ ቤተሰብ እናትየው ደግሞ ህጻኑን መንከባከብ ትችላለች። የተጎዱ ወላጆች አብዛኛውን ጊዜ የሚጠመዱት ከልጃቸው ይልቅ በራሳቸው ችግሮች ነው፤ ይህን ደግሞ መቀበል አለባችሁ። ህጻኑ የአደራ ቤተሰብ ውስጥ እንዲመደብ ያደረገው አንደኛው ችግርም ይኸው ነው።